የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን ዓለም አቀፉን የአካል ጉዳተኞች ቀን በኢትዮጵያ ለ 31ኛ ጊዜ ለማሰብ ከሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይሚኒስቴር እና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በአሶሳ ከተማ ባዘጋጀው መርኃ ግብርላይ ተሳትፎ አድርጓል።

በመርኃ ግብሩ የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን ፕሬዚደንት ሰመረ ማእረ የዕለቱንመሪ ቃል ‘’ለሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ስኬት ትርጉም ያለው ትብብር- ለአካል ጉዳተኞች፣ ከአካል ጉዳተኞች ጋር እና በአካል ጉዳተኞች!‘’ በማስታወስ አካል ጉዳተኞችን ከድህነት ለማውጣት፣ አነስተኛ የሆነውን የአካል ጉዳተኞች የትምህርት ሽፋን ለማሳደግ፣ ለሁሉም መብቶች መሳካት መሣሪያ ሆኖ የሚያገለግለውን የሥራ ስምሪት መብት ለአካል ጉዳተኞች በማረጋገጥ እና በሕግ፣ በፖሊሲና በስትራቴጂ አወጣጥ፣ አተገባበርና ግምገማ ወቅት አካል ጉዳተኞችን ለማሳተፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተገቢውን ጥረት እንዲያደርጉ ለተሳታፊዎች ጥሪ አቅርበዋል።

የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚንስትር ዶ/ር እርጎጌ ተስፋዬ ለፍትሕ ሚኒስቴር የቀረበው ረቂቅ የአካል ጉዳተኞች መብት አዋጅ ግብረ መልስ ተሰጥቶበት ወደ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታቸው የተመለሰ መሆኑን ጠቁመው ረቂቅ አዋጁ ጸድቆ ወደ ትግበራ እንዲገባ ለማስቻል ተጨማሪ ጥረት የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም ለአካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ኢትዮጵያ የአፍሪካ አካል ጉዳተኞች ፕሮቶኮልን ፈርማ የሀገሪቷ የሕግ አካል እንድታደርግ ጥያቄው ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበ መሆኑን አረጋግጠዋል።

የኢሰመኮ የሴቶች፣ የሕፃናት፣ የአካል ጉዳተኞች እና የአረጋውያን መብቶች ኮሚሽነር ርግበ ገብረሐዋሪያ በበኩላቸው ለትምህርት ዕድሜያቸው ከደረሰ አካል ጉዳተኛ ሕፃናት መካከል እጅግ ጥቂቶቹ ብቻ የትምህርት ዕድል ማግኘታቸውን፣ በተለያዩ ቦታዎች በሚከሰቱ ግጭቶች እናመፈናቀሎች ምክንያት በአካል ጉዳተኞች ላይ የሚደርሱ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች በርካታመሆናቸውን፣ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ለመግባት የሚወሰድ አወንታዊ እርምጃ (AffirmativeAction) በመከልከሉ የአካል ጉዳተኞች የትምህርት ተሳትፎ መቀነሱን እንዲሁም በፍትሕ ተደራሽነት ዙሪያ የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችን አብራርተዋል።

ኮሚሽነር ርግበ አከለውም ዓለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞች ቀንን ስናስብ ሊተገበሩ የሚችሉ ግቦችንበማስቀመጥ፣ ቀድሞ ያስቀመጥናቸውን ግቦች ውጤት ይፋ በማድረግ እንዲሁም የአካል ጉዳተኞችን መብቶች ለማስጠበቅ፣ ለማስፋፋት እና ለማስከበር የሚወሰዱ እርምጃዎችን ዘላቂነት በማረጋገጥ ሊሆን እንደሚገባ አጽንዖት ሰጥተው ተናግረዋል። አያይዘውም የዚህን ዓመት ክብረበዓል መሪ ቃል መሠረት በማድረግ የ2030 ዘላቂ ልማት ግቦች አጀንዳ አካል ሆነው ከ8 ዓመታት በፊት እ.አ.አ. 2015 ሥራ ላይ የዋሉት እና ኢትዮጵያ በልማት ዕቅዶቿ በማካተት እየሠራችባቸው ላሉት አስራ ሰባቱ የተባበሩት መንግሥታት ዘላቂ የልማት ግቦች ያልተሸራረፈ ትግበራየሁላችንንም ቁርጠኝነት ይሻል ብለዋል።