የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በፌዴራል ሕገ መንግሥቱ መሠረት ነጻ የፌዴራል መንግሥት አካል ሆኖ በአዋጅ ቁጥር 210/1992 (በአዋጅ ቁጥር 1224/2012 እንደተሻሻለው) የተቋቋመና ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተጠሪ የሆነ፣ ለሰብአዊ መብቶች መስፋፋት፣ መከበር እና ጥበቃ የሚሠራ ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች ተቋም ነው። የኢሰመኮ ማቋቋሚያ አዋጅ አንቀጽ 8 ኢሰመኮ አንድ ዋና ኮሚሽነር እንደሚኖረው ይደነግጋል፡፡ ከሐምሌ ወር 2011 ዓ.ም. እስከ ሰኔ ወር 2016 ዓ.ም. ድረስ ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ኢሰመኮን በዋና ኮሚሽነርነት ያገለገሉ ሲሆን፤ የ5 ዓመታት የሥራ ዘመናቸው መጠናቀቁን ተከትሎ ምክትል ዋና ኮሚሽነር ራኬብ መሰለ የዋና ኮሚሽነርን ሥራዎች ደርበው እየሠሩ ይገኛሉ፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽንን የሚያቋቁሙና ተቋሙን የሚመሩ አባላትን እንዲመርጥና እንዲሰይም በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት በተደነገገው መሠረት፣ የዋና ኮሚሽነሩን ቦታ ለማሟላት ኅዳር 26 ቀን 2017 ዓ.ም. የዕጩዎች ጥቆማ ጥሪ ለሕዝብ ይፋ አድርጓል።
በኢሰመኮ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 210/1992 (በአዋጅ ቁጥር 1224/2012 እንደተሻሻለው) በአንቀጽ 12 መሠረት ዕጩዎች የሚከተሉትን መስፈርቶች ሊያሟሉ ይገባል፦
- ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግሥት ተገዢ የሆነ/ች፣
- ዕድሜ፡- ከ35 ዓመት በላይ፣
- ዜግነት፡- ኢትዮጵያዊ/ት፣
- ለሰብአዊ መብቶች መከበር ተቆርቋሪ የሆነ/ች፣
- ሥራውን ለመሥራት የሚያስችል የተሟላ ጤንነት ያለው/ያላት፣
- ከደንብ መተላለፍ ውጪ ባለ በሌላ ወንጀል ጥፋት ተከሶ/ሳ ያልተፈረደበት/ባት፣
- በሕግ ወይም አግባብ ባለው ሌላ ሙያ የሰለጠነ/ች፣ በልምድ ሰፊ ዕውቀት ያካበተ/ች፣
- በታታሪነቱ/ቷ፣ በታማኝነቱ/ቷ እና በሥነ ምግባሩ/ሯ መልካም ስም ያተረፈ/ች፣
- የማንኛውም ፖለቲካ ድርጅት አባል ያልሆነ/ች፣ እንዲሁም
- ከፍተኛ ኃላፊነት ለመሸከም የሚያስችል የአመራር ብቃት ያለው/ላት፣
በተጨማሪም ለአካል ጉዳተኛ ባለሙያዎች ኢሰመኮ ተመጣጣኝ ማመቻቸት የሚያዘጋጅ በመሆኑ ከላይ የተዘረዘሩትን መስፈርቶች የሚያሟሉ አካል ጉዳተኛ ባለሙያዎች እንዲያመለክቱ ወይም በዕጩነት እንዲጠቆሙ ይበረታታል።
ስለሆነም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ፌስቡክ ገጽ ላይ በተገለጸው መሠረት እስከ ታኅሣሥ 10 ቀን 2017 ዓ.ም. ከቀኑ 11፡30 ሰዓት ድረስ እነዚህን መስፈርቶች የሚያሟሉ ዕጩዎችን ከዚህ በታች በተዘረዘሩት መንገዶች በመጠቆም ወይም በማመልከት ሁሉም ባለድርሻዎች እንዲሳተፉ ኢሰመኮ በድጋሚ ጥሪውን ያቀርባል።
ይህንን የተያያዘውን ቅጽ በመሙላት
- በኢሜል አድራሻ፦ humanrightcnc@hopr.gov.et
- በሞባይል ስልክ ቁጥር፡- +251 969 27 43 43
- በቢሮ ስልክ ቁጥር፡- +251 111 13 49 99 በመደወል ወይም
- በአካል ማቅረብ ለሚፈልጉ፦ አራት ኪሎ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የእንግዳ መቀበያ ቢሮ በተዘጋጀው ዝግ ሳጥን ውስጥ የጥቆማ ወረቀታቸውን ማስገባት ይችላሉ።