የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የአማራ ክልል ምክር ቤት በ6ኛ ዙር፣ 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን፣ 9ኛ መደበኛ ጉባኤ የዳኞች ያለመከሰስ መብት የሕግ ከለላ የሚሰጥ የአማራ ብሔራዊ ክልል ፍርድ ቤቶች የማጠናከሪያ አዋጅ ማጽደቁን እንደ በጎ ጅማሮ ይመለከተዋል። ኢሰመኮ በክልሉ በየደረጃው በሚገኙ ዳኞች ላይ የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን አስመልክቶ በተደጋጋሚ ከደረሱት አቤቱታዎች በመነሳት በክልሉ ያለው የዳኝነት ነጻነት እንዲከበር እና ለዚህም ጠንካራ የሕግ ማዕቀፍ እንዲዘጋጅ ምክረ ሐሳቦችን ማቅረቡ እና ውትወታ ሲያደርግ መቆየቱ የሚታወስ ነው።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ “የዳኝነት ነጻነት ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እና ለሰብአዊ መብቶች መከበር መሠረት በመሆኑ የዳኞች ያለመከሰስ መብት የሕግ ከለላ ማግኘቱ በክልሉ የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ እና ለሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ወሳኝ ነው” ብለዋል። አክለውም አዋጁ እንዲጸድቅ አዎንታዊ ሚና ለተጫወቱ ሁሉ ምስጋና አቅርበው፤ የአዋጁን ውጤታማ አተገባበር ለማረጋገጥ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነት መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል።