የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከኅዳር 28 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ፣ በጋምቤላ ወረዳ (አቦል)፣ በጋምቤላ ከተማ እና በዙሪያው ባሉ አካባቢዎች የተፈጠረውን ግጭትና የጸጥታ መደፍረስ ተከትሎ የተፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችና ሥጋቶችን እየተከታተለ ይገኛል።
ኢሰመኮ ይህ መግለጫ ይፋ እስከተደረገበት ጊዜ ድረስ ባሰባሰበው መረጃ በጋምቤላ ከተማ አስተዳደር የጋምቤላ ከተማ ፖሊስ ጽሕፈት ቤት አዛዥ የነበሩት ዋና ኢንስፔክተር ኡመድ ኡጁሉ መገደልን ተከትሎ በከተማውና በአካባቢው ባሉት ወረዳዎችና ቀበሌዎች ግጭት ተፈጥሮ በተለያዩ አከባቢዎች የተኩስ ልውውጥ ሲካሄድ መቆየቱን፣ በዚህም ሳቢያ የሰዎች ሕይወት መጥፋቱንና የአካል ጉዳት መድረሱን፣ የሰዎችን እና የመጓጓዣ አማራጮችን እንቅስቃሴ የሚገድብ የሰዓት እላፊ በክልሉ መንግሥት መጣሉን፤ ባንኮችንና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችን ጨምሮ በርካታ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት አገልግሎት ማቋረጣቸውን ተገንዝቧል።
በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች የተፈጠረውን ግጭትና የሰላም መደፍረስ በፍጥነት በማስቆም በሰዎች በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደኅንነት፣ ከቦታ ቦታ የመዘዋወር፣ የንብረት፣ የሥራ እንዲሁም ሌሎች ሰብአዊ መብቶች ላይ ተጨማሪ ጥሰቶች እንዳይደርሱ ለመከላከል በቂ የጸጥታ አካላት በአስቸኳይ እንዲሰማሩ እንዲደረግ ኢሰመኮ ያሳስባል።
በክልሉ በተለያዩ ጊዜያት የሚፈጠሩ ግጭቶችን በዘላቂነት ለማስቆም፣ ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ እና ወደፊት ተመሳሳይ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች እንዳይከሰቱ ለመከላከል የፌዴራሉ እና የክልሉ መንግሥታት ተገቢ እርምጃዎችን ሊወስዱ ይገባል። በአካባቢው ተሰሚነት ያላቸው የሀገር ሽማግሌዎችን እንዲሁም የሃይማኖት እና የማኅረሰብ መሪዎችን በማሳተፍ ውይይቶችና ዕርቆች እንዲካሄዱ እንዲሁም ከአጋር ድርጅቶችና ባለድርሻዎች ጋር በትብብር በመሥራት ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች ተገቢውን ሕክምና እና ካሳ እንዲያገኙ እንዲሁም እንዲቋቋሙ ማድረግ ይገባል።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ በጋምቤላ ክልል የሚከሰቱ ግጭቶችና የሰላም መደፍረሶች በክልሉ ያለውን የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ለማሻሻል የሚደረጉ ጥረቶችንና እርምጃዎችን እየተፈታተኑ መሆናቸውን ገልጸው፤ ኢሰመኮ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ በዚህ መግለጫ ያቀረባቸውን እና ከዚህ ቀደም ለፌዴራሉና ለክልሉ መንግሥታት የሰጣቸውን ምክረ ሐሳቦች በተሟላ ሁኔታ እንዲፈጸሙ ማድረግ እንደሚገባ በአጽንዖት ገልጸዋል። በተለይም በግጭቶችና ጥቃቶች ላይ ተሳታፊ የሆኑ ቡድኖች እና ግለሰቦች ላይ ተገቢውን የወንጀል ምርመራ በማድረግ ተጠያቂነት የማረጋገጥ ጥረቶችን የበለጠ አጠናክሮ መቀጠል እንዲሁም የክልሉ የጸጥታ ተቋማት ግጭቶችን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የሚያስችል ብቃት እንዲኖራቸው ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። ዋና ኮሚሽነሩ አክለውም ኢሰመኮ ከመደበኛው የሰብአዊ መብቶች ክትትልና ምርመራ ሥራው ጎን ለጎን፣ ጉዳዩ ከሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት ጋር በመነጋገር ግጭቶች በውይይት እንዲፈቱ ጥረት እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።