በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት ምንድነው?
በቂ መኖሪያ ቤት ለአንድ ግለሰብ ወይም ቤተሰብ የመረጋጋት እንዲሁም አካላዊ እና ሥነ ልቦናዊ ደኅንነት መሠረት ከመሆኑም በተጨማሪ የሰው ልጅ ሰብአዊ ክብሩ ተጠብቆ እንዲኖር እንዲሁም ሌሎች ሰብአዊ መብቶቹን እንዲጠቀም ለማስቻል መሠረታዊ ቅድመ ሁኔታ ነው። በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በተለያዩ የሰብአዊ መብቶች ሰነዶች እውቅና እና ጥበቃ የተሰጠው ሲሆን በይዘቱም ጣሪያ እና ግድግዳ ያለው መጠለያ ከማግኘት ያለፈና ደኅንነት ተጠብቆ በሰላምና በክብር ለመኖር በሚቻልበት ቦታ ላይ የመኖር መብት መሆኑን የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊ እና የባህል መብቶች ኮሚቴ በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን አስመልክቶ የሰጠው አጠቃላይ ትንታኔ ቁጥር 4 ያስረዳል።
በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በዓለም አቀፍ፣ አህጉራዊ እና ሀገራዊ የሕግ ማዕቀፎች የተሰጠው ጥበቃ ምን ይመስላል?
በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በዓለም አቀፍ ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ እውቅና ያገኘው በሁሉ አቀፍ የሰብአዊ መብቶች መግለጫ ሲሆን መግለጫው በአንቀጽ 25(1) ሥር “ማንኛውም ሰው በቂ ምግብ፣ ልብስ፣ መኖሪያ ቤት፣ ሕክምና እና አስፈላጊ የማኅበራዊ አገልግሎቶችን ጨምሮ ለራሱ እና ለቤተሰቡ ጤና እና ደኅንነት በቂ የኑሮ ደረጃ የማግኘት መብት አለው” በማለት ይደነግጋል። በተመሳሳይ ሁኔታም የኢኮኖሚ ፤የማኅበራዊ እና የባሕል መብቶች ዓለም አቀፍ ቃልኪዳን አንቀጽ 11(1) ማንኛውም ሰው በቂ ምግብ፣ ልብስና መኖሪያ ቤትን ጨምሮ ለራሱ እና ለቤተሰቡ በቂ የኑሮ ደረጃ የማግኘት እና የኑሮ ሁኔታውን በቀጣይነት የማሻሻል መብት ያለው መሆኑን እንዲሁም አባል ሀገራት ለመብቱ ዕውቅና መስጠትና ተግባራዊነቱን ለማረጋገጥ ተገቢውን እርምጃ መውሰድ እንደሚጠበቅባቸው ይገልጻል።
ከላይ ከተመላከቱት በተጨማሪም በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በሌሎች ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ስምምነቶች፣ መግለጫዎች እንዲሁም በዓለም አቀፍ የሥራ ድርጅት (ILO) ሰነዶች ሥር እውቅና ተሰጥቶታል። ከነዚህም መካከል የሕፃናት መብቶች ስምምነት አንቀጽ 27(3)፣ ዓለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞች መብቶች ስምምነት አንቀጽ 28(1)፣ አድሎአዊ የዘር ልዩነቶችን ለማስወገድ የተደረገ ዓለም አቀፍ ስምምነት አንቀጽ 5 (ሠ) (iii)፣ በሴቶች ላይ የሚደረግ ማንኛውንም አድሎአዊ ልዩነት ለማስወገድ የተደረገ ዓለም አቀፍ ስምምነት አንቀጽ 14(2) (ሸ)፣ የልማት መብት መግለጫ አንቀጽ 8 እና የዓለም አቀፉ የሥራ ድርጅት የሠራተኞች የመኖሪያ ቤት መብት ምክረ ሐሳብ 1961 (ቁጥር 115) ይገኙበታል። እነዚህ ስምምነቶች እና ሰነዶች ሁሉም ሰው ያለምንም አድሎ በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት እንዳለው እና መንግሥት መብቱን ለማረጋገጥ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ እንዳለበት ደንግገዋል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ በተ.መ.ድ ዘላቂ የልማት ግቦች (እ.ኤ.አ. 2015) ውስጥ በቂ፣ደኅንነቱ የተጠበቀ እና ተመጣጣኝ ዋጋ ያለው መኖሪያ ቤት እና መሠረታዊ ፍላጎቶች ተደራሽነትን ማረጋገጥ በግብ 11 ሥር ተካቶ ይገኛል።
አህጉራዊ የሕግ ማዕቀፍን ስንመለከት የአፍሪካ የሰዎችና ሕዝቦች መብቶች ቻርተርን የመተርጎም ስልጣን የተሰጠው የአፍሪካ የሰዎችና ሕዝቦች መብቶች ኮሚሽን በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በግልጽ እውቅና ካገኙ ሌሎች መብቶች ማለትም በአንቀጽ 14 ከተካተተው የንብረት ባለቤትነት መብት፣ በአንቀጽ 16 ከተካተተው የጤና መብት፣ በአንቀጽ 18(1) ከተካተተው የቤተሰብ ጥበቃ መብት እና በአንቀጽ 24 ከተካተተው ለእድገት ተስማሚ የሆነ አካባቢ የማግኘት መብት ጣምራ ንባብ መሠረት በተዘዋዋሪ ዕውቅና የተሰጠው መብት መሆኑን ትርጓሜ ሰጥቶበታል። ሌሎች አህጉራዊ ስምምነቶችም በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን በተለያየ መልኩ እውቅና የሰጡ ሲሆን ከነዚህም መካከል የአፍሪካ የሕፃናት መብቶች እና ደኅንነት ቻርተር እና የአፍሪካ የሰዎችና ሕዝቦች መብቶች ቻርተር የሴቶች መብቶች ፕሮቶኮል (ማፑቶ ፕሮቶኮል) ተጠቃሾች ናቸው።
በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በሀገራዊ የሕግ ማዕቀፍ የተሰጠውን ጥበቃ ስንመለከት ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ፤ የማኅበራዊ እና የባሕል መብቶች ዓለም አቀፍ ቃልኪዳንን በ1993 ዓ.ም. ያጸደቀች እንደመሆኗ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ መንግሥት አንቀጽ 9(4) መሠረት ስምምነቱ የሀገሪቱ የሕግ አካል በመሆን በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን የማረጋገጥ ግዴታ በመንግሥት ላይ ይጥላል፡፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ሕገ መንግሥት በአንቀጽ 41(3) ላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በመንግሥት ገንዘብ በሚካሄዱ ‘ማኅበራዊ አገልግሎቶች’ በእኩልነት የመጠቀም መብትን ሲደነግግ፤ አንቀጽ 41(4) መንግሥት ‘ማኅበራዊ አገልግሎቶችን’ ለሕዝብ ለማቅረብ በየጊዜው እየጨመረ የሚሄድ ሃብት የመመደብ ግዴታ እንዳለበት ይደነግጋል። በእነዚህ ድንጋጌዎች ሥር ‘ማኅበራዊ አገልግሎቶች’ የሚለው ቃል መኖሪያ ቤትን የሚያካትት ተደርጎ ሊተረጎም የሚችል ነው፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የአካልና የአዕምሮ ጉዳተኞችን፣ አረጋውያንንና ያለወላጅ ወይም ያለአሳዳጊ የቀሩ ሕፃናትን ለማቋቋም እና ለመርዳት የሚያስችል ግብአት መንግሥት አቅም በፈቀደው ደረጃ የመመደብ ግዴታ እንዳለበት ሕገ መንግስቱ በአንቀጽ 41(5) ላይ ይደነግጋል። ስለሆነም ለእነዚህ የማኅበረሰብ ክፍሎች አስፈላጊ ሆኖ እስከተገኘ ድረስ ማቋቋም እና መርዳቱ የመኖሪያ ቤት አቅርቦትን ሊያካትት እንደሚችል መገንዘብ ይቻላል፡፡ በሕገ መንግሥቱ መኖሪያ ቤት በግልፅ የተጠቀሰው ብሔራዊ የፖሊሲ መርሖች እና ዓላማዎችን በሚዘረዝረው ምዕራፍ ውስጥ በአንቀጽ 90(1) ላይ ሲሆን በዚህ ድንጋጌ መሠረት ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሀገሪቱ አቅም በፈቀደ መጠን መኖሪያ ቤት እንዲኖረው እንደሚደረግ ይደነግጋል፡፡
ከሕገ መንግሥቱ በተጨማሪ ከበቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት መጠበቅ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ሌሎች ዝርዝር ሀገራዊ ሕጎች ያሉ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል ለሕዝብ ጥቅም ሲባል የመሬት ይዞታ የሚለቀቅበት፣ ካሣ የሚከፈልበት እና ተነሽዎች መልሰው የሚቋቋሙበትን ሁኔታ ለመወሰን የወጣ አዋጅ ቁጥር 1161/2011 (በአዋጅ ቁጥር አዋጅ ቁጥር 1336/2016 እንደተሻሻለው) እና አዋጁን ለማስፈጸም የወጣው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 472/2012 ፤ የመኖሪያ ቤት ኪራይ ቁጥጥር እና አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 1320/2016፤የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የጋራ ሕንጻ ቤት ባለቤትነት አዋጅ ቁጥር 370/1995 እንዲሁም የኢትዮጵያ የሕንጻ አዋጅ ቁጥር 1356/2017 ይገኙበታል።
በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት ዋና ዋና ይዘቶች ምን ምን ናቸው?
የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊ እና የባሕል መብቶች ኮሚቴ በአጠቃላይ ትንታኔ ቁጥር 4 ሥር በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን ዋና ዋና ይዘቶች በዝርዝር ያስቀመጠ ሲሆን እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፦
- የይዞታ ዋስትና (Legal security of tenure)፦ ማንኛንውም ሰው ከመኖሪያ ቤቱ በግዳጅ ከመፈናቀል፣ ከትንኮሳና ከሌሎች ስጋቶች ጥበቃ የሚያደርግለት በቂ የሕግ ዋስትና ሊኖረው ይገባል።
- የአገልግሎቶች፣ የቁሳቁሶች፣ የመገልገያዎች እና የመሠረተ ልማት ተገኝነት (Availability of services, materials, facilities and infrastructure)፦ በቂ መኖሪያ ቤት ለጤና እና ደኅንነት አስፈላጊ የሆኑ መገልገያዎች ሊኖሩት ይገባል። ይህም እንደ ንጹህ የመጠጥ ውሃ፣ የምግብ ማብሰያ፣ ኤሌክትሪክ፣ የቆሻሻ እና የፍሳሽ ማስወገጃ አገልግሎቶች ተገኚ መሆንን ይጠይቃል።
- ተመጣጣኝነት (Affordability)፦ ከመኖሪያ ቤት ጋር የተያያዙ ወጪዎች ሌሎች መሠረታዊ ፍላጎቶችን የማሟላት ዐቅምን የሚገድቡ መሆን የለባቸውም። በመሆኑም መንግሥት ከመኖሪያ ቤት ጋር የተያያዙ ወጪዎች ከሰዎች የገቢ መጠን ጋር ተመጣጣኝነት እንዲኖራቸው ምክንያታዊ ያልሆኑ የቤት ኪራይ ጭማሪዎችን መከልከልን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ እርምጃዎችን መውሰድ ይጠበቅበታል።
- ለኑሮ ተስማሚነት (Habitability)፦ በቂ መኖሪያ ቤት በቂ ስፋት ያለው እንዲሁም ለነዋሪዎቹ ከቅዝቃዜ፣ ከእርጥበት፣ ከሙቀት፣ ከዝናብ፣ ከንፋስ ወይም ከሌሎች የጤና ስጋቶች እና አደጋዎች በቂ ጥበቃ በማድረግ ለኑሮ ተስማሚ መሆን አለበት።
- ተደራሽነት (Accessibility)፦ መኖሪያ ቤት ለሁሉም ሰው ተደራሽ መሆን ያለበት ሲሆን በተለይም ለመብት ጥሰቶች ተጋላጭ የሆኑ የማኅበረሰብ ክፍሎች ትኩረት ሊሰጣቸውና የመኖሪያ ቤት የሕግ እና የፖሊሲ ማዕቀፎች የእነዚህን ማኅበረሰቦች ልዩ ፍላጎት ከግምት ውስጥ ማስገባታቸውን ማረጋገጥ ያስፈልጋል።
- መገኛ ቦታ (Location)፦ በቂ መኖሪያ ቤት ለሥራ አማራጮች፣ ለጤና እንክብካቤ አገልግሎቶች፣ ለትምህርት ቤቶች፣ ለሕፃናት ማቆያ ማዕከላት እና ለሌሎች አስፈላጊ ማኅበራዊ አገልግሎቶች ተደራሽ በሆነ አካባቢ መገኘት ይኖርበታል።
- የባሕል በቂነት/ተኳኋኝነት (Cultural adequacy)፦ ቤቶች የሚገነቡበት መንገድ፣ ጥቅም ላይ የሚውሉ የግንባታ ቁሳቁሶች እና ይህን የሚመለከቱ የፖሊሲ ማዕቀፎች የባሕል ማንነት መገለጫዎችን እና ብዝኃነትን በአግባቡ ለመግለጽ የሚያስችሉ መሆን ይኖርባቸዋል።
በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን አስመልክቶ የመንግሥት ግዴታዎች ምንድን ናቸው?
በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በሀገራት ላይ የማክበር፣ የመጠበቅ እና የማሟላት ግዴታዎችን ይጥላል። የማክበር ግዴታ መንግሥት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የመብት ባለቤቶች መብታቸውን ሲጠቀሙ ተገቢ ያልሆነ ጣልቃ ገብነት ከማድረግ እንዲቆጠብ ይጠይቃል። ይህም ለምሳሌ ከበቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት ጋር በተያያዘ መንግሥት ሰዎችን ከመኖሪያ ቤታቸው በኃይል ከማስነሳት/ከማፈናቀል ድርጊት መቆጠብ ያለበት መሆኑን እንደሚያመላክት የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊ እና የባህል መብቶች ኮሚቴ በአጠቃላይ ትንታኔ ቁጥር 4 ላይ ይገልጻል። የመጠበቅ ግዴታ መንግሥት የመብት ባለቤቶች መብታቸውን ሲጠቀሙ ሦስተኛ ወገኖች ጣልቃ እንዳይገቡ የሚከለክሉ እርምጃዎችን እንዲወስድ ግዴታ የሚጥል ነው። የመብት ባለቤቶች በሦስተኛ ወገኖች ከሚደርስባቸው የመብት ጥሰቶች ለመጠበቅ አስፈላጊ እርምጃዎችን አለመውሰድ እንዲሁም መብቶቹ ተጥሰው ሲገኙ መፍትሔ አለመስጠት ይህን ግዴታ መጣስ ሆኖ ይቆጠራል። የማሟላት ግዴታ በበኩሉ በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን ለመጠቀም የሚያስችሉ ሁኔታዎችን የማመቻቸት፣ የማቅረብ እና መብቱን የማሳደግ ወይም የማስተዋወቅ ግዴታዎችን ያጠቃልላል። በዚህም መሠረት መንግሥት በቂ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብትን ሙሉ በሙሉ እውን ለማድረግ አስፈላጊ የሕግ፣ የአስተዳደር፣ የበጀት፣ የዳኝነት እና ሌሎች እርምጃዎችን መውሰድ ይጠበቅበታል።