የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በቤኒንሻንጉል ጉምዝ ክልል፣ ከማሺ ዞን የሚገኘውና ከሃያ አምስት ሺህ በላይ ነዋሪዎች የሚገኙበት የሴዳል ወረዳ ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ፣ ከሚያዝያ 11 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ በታጣቂዎች ቁጥጥር ስር መዋሉን የደረሱት መረጃዎች ያመላክታሉ። በርካታ ነዋሪዎች፣ የወረዳው አስተዳደር እና ፖሊስ አካባቢውን ጥለው ወደ ተለያዩ ስፍራዎች መሸሻቸውን ኮሚሽኑ ተረድቷል። ታጣቂ ቡድኑ የመንግስት እና የግለሰብ ንብረቶችን ማቃጠሉን፤ ነዋሪችን፣ የወረዳውን እና የዞን አመራሮችን እንዲሁም የመንግስት ሰራተኞችን መግደሉን እና ማገቱም ተገልጿል። ኢሰመኮ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች በአቅራቢያው ያለው የፀጥታ ኃይል ከአቅሙ በላይ እንደሆነና ተጨማሪየተላከው ኃይልም ወደ አካባቢው እንዳልደረሰ ይገልጻሉ።

ይህ ክስተት በክልሉ የቆየው የጸጥታ ችግር እየተባባሰና መልኩን እየቀየረ መምጣቱን የሚያሳይ በመሆኑ ከፍተኛ ስጋት የሚያሳድር ነው። ኢሰመኮ ጉዳዩን በቅርበት እየተከታተለሲሆን፣ ከሚመለከታቸው የፌዴራል እና የክልል መንግስት አካላት ጋር በመነጋገር ላይ ነው። ኮሚሽኑ መንግስት በአፋጣኝ የአካባቢው እና የክልሉን የፀጥታ ኃይል እንዲያጠናክርና እና ተጨማሪ የሰዎች ሞት እና የከፋ ሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንዳይከሰት እንዲከላከል ጥሪውን ያቀርባል::