Download
Download is available until [expire_date]
  • Version
  • Download 9
  • File Size 1.11 MB
  • File Count 1
  • Create Date March 7, 2024
  • Last Updated April 8, 2024

የፍርድ ቤቶች እና ፍትሕ ጽሕፈት ቤቶች ለአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን የተደራሽነት ሁኔታ ሪፖርት

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ፍርድ ቤቶች እና የፍትሕ ጽሕፈት ቤቶች ለአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን ባላቸው ተደራሽነት ላይ ያተኮረ ባለ 31 ገጽ የሰብአዊ መብቶች ክትትል ሪፖርት ይፋ አድርጓል። የዚህ የክትትል መነሻ በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ የተመረጡ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከባቢያዊ ተደራሽነት ላይ ከግንቦት 23 እስከ 24 ቀን 2014 ዓ.ም. ተደርጎ የነበረው ክትትል ሲሆን፣ በዚህም የፍርድ ቤቶቹ ሕንጻዎችና ምድረ-ግቢዎች ያላቸው የከባቢያዊ ተደራሽነት ክፍተት የፍትሕ ሥርዓት ተደራሽነት መብትን ለማረጋገጥ ተግዳሮት መሆኑን ለመረዳት ተችሏል።

ኮሚሽኑ የክትትል ሥራውን በማስፋት የፍርድ ቤቶችና የፍትሕ ጽሕፈት ቤቶች ሁለንተናዊ ተደራሽነትን በተመለከተ በተመረጡ በአፋር፣ በአማራ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በኦሮሚያ፣ በሶማሊ እና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሎች በሚገኙ የፍትሕ ተቋማት ከታኅሣሥ 17 እስከ 22 ቀን 2015 ዓ.ም. እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ የፌዴራል ፍትሕ ተቋማት ላይ ከታኅሣሥ 24 እስከ ጥር 6 ቀን 2015 ዓ.ም. የሰብአዊ መብቶች ክትትል አከናውኗል። በሪፖርቱም የክትትሉ ግኝቶች፣ መልካም ጅማሮዎች እንዲሁም የፍትሕ ተቋማት ለአካል ጉዳተኞችና አረጋውያን ያላቸውን ተደራሽነት እና አካታችነት ለማሻሻል የሚያስችሉ ዝርዝር ምክረ ሐሳቦች ቀርበዋል።

ኢሰመኮ በክትትሉ አካል ጉዳተኛ ባለሞያዎችን ያካተተ ቡድን በማሰማራት ከአካል ጉዳተኞችና አረጋውያን፣ ከፍርድ ቤቶችና ፍትሕ ጽሕፈት ቤቶች ኃላፊዎችና ሠራተኞች፣ ከአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን ማኅበራት እንዲሁም የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ መሥሪያ ቤቶች ኃላፊዎችና ሠራተኞች ጋር በተደረጉ ቃለ መጠይቆች፣ በአካል ምልከታ እና ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ሰነዶች በማመሳከር መረጃዎችና ማስረጃዎችን ሰብስቧል። በክትትሉ በአጠቃላይ ከ177 ሰዎች ጋር ቃለ መጠይቅ ተደርጔል፤ ከእነዚህም መካከል 39 አካል ጉዳተኞች እና 20 አረጋውያን በቃለ መጠይቁ ተሳትፈዋል።

አንኳር ጉዳዮች:- የፍርድ ቤቶች እና ፍትሕ ጽሕፈት ቤቶች ለአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን የተደራሽነት ሁኔታ ሪፖርት