የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን በኅዳር ወር 2017 ዓ.ም. የመብቶች እና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል፣ የሕግ ባለሙያዎች ለሰብአዊ መብቶች እና ስብስብ ለሰብአዊ መብቶች በኢትዮጵያ የተባሉ 3 በሰብአዊ መብቶች ዙሪያ የሚሠሩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ላይ ጥሎት የነበረውን እገዳ ካነሳ በኋላ በታኅሣሥ ወር 2017 ዓ.ም. የመብቶች እና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል እና የሕግ ባለሙያዎች ለሰብአዊ መብቶችን በድጋሚ እንዲሁም የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ እና የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ማእከልን ማገዱ ይታወሳል።

ኢሰመኮ ታኅሣሥ 18 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው ጋዜጣዊ መግለጫ በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ላይ የሚተላለፉ እገዳዎች በሲቪል ምኅዳሩ እና በማኅበር የመደራጀት መብቶች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እንዳይፈጥሩ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ አሳስቧል። በተጨማሪም ኢሰመኮ በድርጅቶቹ እገዳ ላይ ሰፊ የሰብአዊ መብቶች ምርመራ ያከናወነ ሲሆን የደረሰባቸውን ግኝቶች እና ምክረ ሐሳቦች ለሚመለከታቸው አካላት አጋርቷል። ኢሰመኮ በተለይም አዲስ በተሾሙት ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ በኩል ጉዳዩን በልዩ ትኩረት በመከታተል ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን እና እገዳ ከተጣለባቸው የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶችን በማድረግ ለጉዳዩ መፍትሔ ለማስገኘት ሢሠራ ቆይቷል።

ይህ የኢሰመኮ ጥረት ውጤት በማስገኘቱ በ4ቱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ላይ ተጥሎ የነበረው እገዳ ከዛሬ የካቲት 24 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ የተነሳ በመሆኑ ኢሰመኮ የተሰማውን ደስታ እየገለጸ በሂደቱ ተባባሪ ለነበሩት የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን እና ሌሎች የመንግሥት አካላት እንዲሁም ለአራቱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምስጋና ያቀርባል። በዚህ አጋጣሚ የሚከሰቱ ችግሮችን የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ እና ሀገራዊ ጥቅምን በማስቀደም በመቀራረብ እና በመወያየት የመፍታት ልምዳችን እንዲጎለብት ኢሰመኮ ጥሪውን ያቀርባል።

ለእንግሊዝኛው ጋዜጣዊ መግለጫ እዚህ ይጫኑ (English)